- ሥራ እና ሥራ ፈላጊ ምሩቃኖች የሚገናኙበት ሀገር አቀፍ የሥራ አውደ ርዕይ ሊካሄድ መሆኑ ተሰማ፡፡
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከደረጃ እና ማስተር ካርድ ፋውንዴሽን ጋር በመተባበር ያዘጋጁት ሥራ እና ሰራተኛ የሚገኛኝበት አውደ ርዕይ ጥቅምት 7 እና 8/2016 ዓ.ም በሚሊኒየም አዳራሽ ይካሄዳል ተብሏል፡፡
በሥራ በአውደ ርእዩ በ2015 ዓ.ም የተመረቁ ከ20 ሺህ በላይ ተማሪቂዎች እና ከ200 በላይ ቀጣሪ ድርጅቶችም እንደሚገኙ ገልፀዋል ፡፡
በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የሀገር ውስጥ ሥራ ሥምሪት ማስፋፊያ ዴስክ ኃላፊ የሆኑት ደጀኔ በቀለ አውደ ርዕዩ ዋና ዋና አላማዎችን በተመለከተ "አሰሪዎች እና ሥራ ፈላጊ ምሩቃን ወጣቶች በግንባር በማገናኘት የቅጥር ምልመላ እና ቅጥር የሚፈጸምበት ነው" ብለዋል፡፡
ኢትዮ ጆብስ (ethio jobs) እና ደረጃ ዶት ኮም (Dereja.com) የሚያስተዳድረው የአፍሪካ ጆብስ ኔትወርክ ቺፍ ኦፕሬቲንግ አፊሰሯ ዲና መኮንን እንደተናገሩት " ደረጃ ዶት ኮም (dereja.com) በተመራቂዎችና በአሰሪዎች መካከል ድልድይ ሆኖ በመስራት ላይ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።
በዚህ አውደ ርዕይም ሥራ ፈላጊ ምሩቃኖች በድርጅቶች ውስጥ ያሉ ክፍት የሥራ ቦታዎች መረጃ የሚያገኙበት፣ የቀጣሪዎች ግንዛቤ የሚያሳድጉ የፓናል ውይይቶች ይካሔዳል ተብሏል።
በመርሀ ግብሩ ስራ ፈላጊዎች ስልጠናዎች የሚያገኙበት ፕሮግራሞችም እንደሚከናወን ዲና መኮንን ሲናገሩ ተደምጠዋል ፡፡
የአፍሪካ ጆብስ ኔትወርክ ቺፍ አፕሬሽን ዳይሬክተር ሲሃም አየለ በበኩላቸው፤ ባለፉት 5 ዓመታት ደረጃ 78 ሺህ የሚሆኑ ምሩቃን ወጣቶች የሥራ ዕድል እንድያገኙ ማስቻሉን ጠቁመው በዚህ አውደ ርዕይም ቀጣሪ ድርጅቶች መቅጠር ስለሚፈልጉት ምሩቃን ብዛትና የሙያ አይነት አስቀድሞ መረጃ ለመውሰድ ተሞክሯል ብለዋል፡፡
ደረጃ ዶት ኮም( dereja.com) ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚገኙ ዩንቨርስቲዎች ጋር በቅንጅት እየሰራ እንደሚገኝ የገለጹት ዳይሬክተሯ ሲሀም አየለ፣ ከ100 ሺህ በላይ ሥራ ፈላጊዎች በደረጃ ዶት ኮም ዌብሳይት ላይ ተመዝግበው ደረጃውን የጠበቀ የስራ ማመልከቻ (cv) ማዘጋጀት ችለዋል ብለዋል፡፡
በዚህም ሥራ ፈላጊዎች በቀላሉ ባሉበት አካባቢ ሁነው ስራ እንዲገናኙ ይደረጋል ማለታቸውን ሰምተናል ፡፡( ንጋት ፕሬስ)
